የሰንደቅ ዓላማ ቀን መከበሩ በሀገሪቱ የተፈጠረውን ብሄራዊ መግባባት ይበልጥ እንደሚያጠናከረው የአማራ ክልል የሴቶችና የወጣቶች ማህበራት አስታወቁ።
የክልሉ ሴቶች ማህበር ዋና ጸሐፊ ወይዘሮ ማሪቱ ፈንታሁን ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንደገለጹት የሰንደቅ ዓላማ ቀን መከበር በሀገሪቱ የተገነባ ያለውን የልማት፣ የሰላምና የዴሞክራሲ ስርዓት ለማጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው።
በዓሉ በሀገር አቀፍ ደረጃ መከበሩ ለሰላም፣ ለልማትና ለዲሞክራሲ የቆመውን የሰንደቅ ዓላማ መርህ ለመዘከርና ከትውልድ ወደ ትውልድ ለማስተላለፍ የላቀ ፋይዳ እንዳለው ዋና ጸሐፊዋ ተናግረዋል።
በመከባበር ላይ የተመሰረተውን የብሄር፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ አንድነትና ብሄራዊ መግባባት ለማጠናከር እንደሚረዳም አመልክተዋል።
በተለይ ጾታዊ መብታቸው እንዲከበር ህገ-መንግስታዊ ዋስትና ላገኙት ሴቶች በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከበረው የሰንደቅ ዓላማ ቀን ልዩ ትርጉም አለው ያሉት ወይዘሮ ማሪቱ፣ የማህበሩ አባላት ዕለቱን በልዩ ድምቀት እንደሚያከብሩት አስታውቀዋል።
የአማራ ወጣቶች ማህበር ሊቀመንበር ወጣት መንግስቱ በላይ በበኩሉ የሰንደቅ ዓላማ ቀን መከበር የሀገሪቱን መልካም ገጽታ ከትውልድ ወደ ትውልድ ለማስተላለፍና የሀገር ፍቅር ስሜትን ለወጣቱ ትውልድ ለማውረስ እንደሚስችል ገልጿል።
የሰንደቅ ዓላማ ቀን ወጣቱ ትውልድ በአዲሱ ሚሌኒየም ድህነት ለማስወገድ ተግቶ እንዲሰራ ከፍተኛ የመነሳሳትና የሀገር ፍቅር ስሜት የሚፈጥር መሆኑንም ወጣት መንግስቱ ገልጿል።
(source: ENA)